ግንቦት 22 ቀን 1997 ዓ.ም.
ለቦርዱ የቀረቡ አቤቱታዎች በጥምር ኮሚቴዎች ሊጣሩ ነው
ግንቦት 22 ቀን 1997 ዓ.ም. በተደረገው የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ መድረክ መደበኛ ስብሰባ ላይ በኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ አነሳሽነት ከፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ከውጭ ታዛቢዎች እና ከቦርዱ ተወካዮች የተውጣጡ ጥምር ኮሚቴዎች በአፋጣኝ እንዲዋቀሩና ለቦርዱ የቀረቡትን አቤቱታዎች እንዲያጣሩ ስምምነት ላይ ተደረሰ፡፡
“አብዛኞቹ የቀረቡት አቤቱታዎች ግልፅነት የሚጎድላቸውና በማስረጃ ያልተደረገፉ ናቸው” ሲሉ አቶ ከማል በድሪ የብሔራዊ የምርጫ ቦርድ ሊቀመንበር ገልፀዋል፡፡ “ቦርዱ በመጀመሪያ የቀረቡለትን አቤቱታዎች ያጤናል፡፡ ከዚያም ችግሮችን ለይቶ አውጥቶ መጣራት የሚያሰፈልገውን ክስ ለሚዋቀሩ አጣሪ ኮሚቴዎች ያስታውቃል” በማለት አብራርተዋል፡፡
ቦርዱ እስከሚመጣው አርብ ግንቦት 26 ቀን 1997 ዓ.ም. ድረስ ሁሉም አቤቱታ ያቀረቡ የፖለቲካ ፓርቲዎች ማስረጃቸውን እንዲያቀርቡ ጠይቋል፡፡
አጣሪ ኮሚቴዎች ለቦርዱ በምርመራ ያገኙትን ውጤት ሲያቀርቡ ቦርዱ የመጨረሻውን ውሳኔ እንደሚሰጥ አቶ ከማል ተናግረዋል፡፡
በምርጫ ሕጉ አንቀጽ 52 (2) መሠረት ቦርዱ ማንኛውም አዋጁን የሚጥስ ተግባር በስፋቱና በዓይነቱ የምርጫውን ውጤት እንደሚወስን በራሱ ክትትል ወይም ከተወዳዳሪዎች ወይም ተወዳዳሪዎችን ካቀረበ ፓርቲ በቂ መረጃ ካገኘ የምርጫውን ሂደት ለማቆም ወይም የምርጫውን ውጤት ውድቅ ለማድረግና እንደገና ምርጫ እንዲካሄድ ለማዘዝ ይችላል፡፡ ይህንን መሠረት አድርጎ ቦርዱ ውሳኔዎችን እንደሚያሳልፍ ተገልጿል፡፡
በአጣሪ ኮሚቴዎች የቀረቡትን የምርመራ ውጤቶች ቦርዱ ካየ በኋላ ጊዜያዊ የምርጫ ውጤቱን ሊያፀናው ወይንም ዳግም ምርጫ እንዲካሄድ ሊወስን ይችላል፡፡
ድጋሚ ምርጫ እንዲደረግ የሚወሰነው የተከሰቱት ችግሮች በተጠቀሱት የምርጫ ክልሎች ውጤት ላይ ወሳኝነት ካላቸው ብቻ እንደሚሆን የቦርዱ ሰብሳቢ አመልክተዋል፡፡
አንዳንድ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በጋራ መድረኩ ውይይት ላይ ሰኔ 1 ቀን 1997 ዓ.ም. ቦርዱ ይፋ ሊያደርግ ያቀደውን የምርጫ ውጤት እንዲያራዝም ጠይቀዋል፡፡ በተጨማሪም የምርጫ ቦርድ ጽሕፈት ቤት እያስታወቀ ያለው የጊዜያዊ የምርጫ ውጤት እንዳይቀጥል ጠይቀዋል፡፡
አቶ ከማል ቦርዱ የምርጫውን ውጤት ይፋ የሚያደርግበትን ቀን እንዲራዘም የተጠየቀውን ጥያቄ ለቦርዱ እንደሚያቀርቡና ቦርዱ እንደሚወስንበት ተናግረዋል፡፡
“ቦርዱ ተገቢ ነው ብሎ ካመነበት ቀኑ ይራዘማል፡፡ እስከመቼ መራዘም እንዳለበት ቦርዱ ያስታውቃል” በማለት አቶ ከማል ገልፀዋል፡፡
የቦርዱ ሊቀመንበር ጊዜያዊ የምርጫ ውጤት እንዳይገለፅ የሚለውን ሃሣብ ውድቅ አድርገዋል፡፡ ጊዜያዊ የምርጫ ውጤት መነገሩ ቦርዱ በግልፅነት እንደሚሰራ የሚያሳይና ሕዝቡን ለማስገንዘብ ይጠቅማል ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ እስካሁን ከ200 በላይ በሚሆኑ የምርጫ ክልሎች ላይ አቤቱታዎች ቀርበውለታል፡፡
ለበለጠ መረጃ በእነዚህ ቁጥሮች ይደውሉ፡፡
የፕሬስ ኦፊሰር ጌታሁን አሞኘ 251 - 9 - 643738
ረዳት ፕሬስ ኦፊሰር ሕይወት አለማየሁ 251 - 9 - 487576
|