ሐምሌ 1 ቀን 1997 ዓ.ም.
የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ የ307 የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የምርጫ ውጤት ይፋ አደረገ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ የ307 የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የምርጫ ውጤት አረጋግጦ በዛሬው ዕለት ይፋ አደረገ፡፡
በቦርዱ ይፋ የተደረገው ውጤት ምንም አይነት አቤቱታ ያልቀረበባቸው እና አቤቱታ ቀርቦባቸው በቅሬታ ሰሚ አካሉ እና በቦርዱ በድጋሚ ውድቅ የተደረጉትን የምርጫ ክልሎች ያጠቃልላል፡፡ ቀሪዎቹ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና የክልል ምክር ቤት አባላት የምርጫ ውጤት በቀጣይ ሳምንታት ይፋ ይደረጋል፡፡
የቦርዱ ሰብሳቢ አቶ ከማል በድሪ እንዳሉት በ140 የምርጫ ክልሎች የማጣራት ሥራ እያከናወኑ ያሉት የአቤቱታ አጣሪ ኮሚቴዎች በሚቀጥለው ሳምንት ሥራቸውን አጠናቀው ይመለሳሉ፡፡ የቦርዱ አጣሪ ኮሚቴዎች በሚያቀርቡት የውሣኔ ሃሣብ መሠረት የመጨረሻ ውሳኔ እንደሚሰጥ የገለፁት አቶ ከማል ውሣኔው ጊዜያዊ ውጤቱን ማፅናት ወይም በምርጫ ክልሉ በሚገኙ የምርጫ ጣቢያዎች በሙሉ ወይም በከፊል ዳግም ምርጫ ማካሄድ ሊሆን እንደሚችል ጠቁመዋል፡፡
የቦርዱ የቅሬታ ሰሚ አካል በ64 የምርጫ ክልሎች ላይ የአቤቱታ መስማት ሥራውን በሚቀጥለው ሳምንት ካጠናቀቀ በኋላ ለሁለተኛ ጊዜ ታይቶ ምርመራ እንዲደረግባቸው የተወሰኑት የምርጫ ክልሎች ቀደም ሲል በቦርዱ እንዲመረመሩ ከተወሰኑት 14 የምርጫ ክልሎች ጋር በጋራ እንደሚጣሩ አቶ ከማል ገልፀዋል፡፡ ለሁለተኛ ጊዜ ታይተው ተቀባይነት ያላገኙ አቤቱታዎችም በይፋ የሚገለፁ ይሆናሉ፡፡
23 የምርጫ ክልሎች ያሉት የሱማሌ ክልል ምርጫም በነሐሴ ወር የሚካሄድ ሲሆን ውጤቱም በሁለት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ይገለፃል፡፡ በዛሬው ዕለት ይፋ በተደረገው የ307 የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የምርጫ ውጤት ኢህአዴግ 139 መቀመጫዎችን በማግኘት እየመራ ሲሆን ቅንጅት ለአንድነትና ለዲሞክራሲ 93፣ የኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ ኃይሎች ሕብረት 42 መቀመጫዎችን በማግኘት ይከተላሉ፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ የ524ቱን የምርጫ ክልሎች ውጤት በዛሬው ዕለት ይፋ ለማድረግ ዕቅድ የነበረው ቢሆንም የቀረቡ አቤቱታዎች መብዛትና የማጣራት ሂደቱ ጊዜ መውሰድ አጠቃላይ ውጤቶቹን ለመግለጽ አላስቻለውም፡፡
ለበለጠ መረጃ በእነዚህ ቁጥሮች ይደውሉ፡፡
የፕሬስ ኦፊሰር ጌታሁን አሞኘ 251 - 9 - 643738
ረዳት ፕሬስ ኦፊሰር ሕይወት አለማየሁ 251 - 9 - 487576 |